Tuesday, July 29, 2014

ወይኖና እኔ/

ሰፈራችን ምናብ ሆቴል እሚባል ቀውጢ ሆቴል አለ ፡ ታዲያ ብዙ ጊዜ ጥቂትአመሻሽቼ እገባለሁ እያልኩ እዛው እየነጋብኝ ተቸግሪያለው ፡ እንደውም የሆነ ቀን ከጋለ ጭፈራ ላይ አቋርጨ ሽንት ልደፋ በሩን ገፋ ሳደርግ ለካ ነግቶ ኖሮ አዳሜ ለስራ እየተሯሯጠ ምድረ ወያላ ‹‹ቄራ ሜክሲኮ ፤ ሜክሲኮ ናችሁ?›› ሲል አይኔን ማመን አቅቶኝም ያውቃል፡፡
እንደምታዩት ምናብ ሆቴል ስሙ ይገርማል ፡ እንደ ስሙ ቤቱም ገራሚ ነው እረ፡ ምግቡ ሁሉ (እኔ በልቼ አላቅም እንጂ) ገራሚ ነው አሉ ፡ ስለመጠጡ እንኳን ለኔ ተውት እንደው ሀገራችን ኋላ ቀር በመሆኗ የአመቱ ምርጥ ጠጭ ምናምን ተብሎ አመታዊ ሽልማት የለም እንጂ ቢኖር ኖሮ እኔ ነበርኩ ዋንጫውን በየአመቱ በሁለት እጄ ከፍ እማደርገው ፡ ግን ምን ዋጋ አለው እንደስሙ ምኞቴ ሁሉ ምናብ ሆኖ ቀረ፡፡
ሜሮን ፣ ሜላት ፣ ሄሮን ፣ ሄለን ምናምን እሚባሉ የቅንጦት ስሞች እኛ ሰፈር አይዘወተሩም ፡ ይልቁኑ ባርች ፡ ቀዮ ፡ ወይኖ የተባሉ ተቀፅላ ስሞች ይበረክታሉ ፡ እነዚህ ስሞች ታዲያ አብዝሀኛውን ጊዜ ከስም ከለር እና አኳኋን ጋር ተያይዘው የሚወጡ ናቸው፡፡ እንዳንዴ እንደውም ዝንጀርና አይጦ ሁሉ እሚባሉ ስሞች እሚወጡበት ዘመን አለ እንዳልኳችሁ ይኸም ከመልክ ጋር ተያይዞ የሚወጣ ስም ነው ለምሳሌ ለምን አይጦ እሚባል ስም አወጣችሁ ብላችሁ አትጠይቁም እንጂ ከጠየቃችሁ ልጂቷ አንዳች የሆነ አይጥማ ከለር የተላበሰች ሲሆን ባጭሩ ታዲያ አይጦ እንላታለን ስትቆላመጥ (ድንቄም ቁልምጫ)፡፡
እንደለመድኩት ምናብ ሆቴል ሄጄ ካልተቀመጥኩ እሚያመኝ ሁሉ ስለሚመስለኝ ባይኖረኝ እራሱ ያው በክሬዲትም ቢሆን ፉት ሳልል አልገባም ፡ ከስራ እንደወጣሁ የሆነ ቀን ከሚያካፋው ዝናብ ለመሸሽም ቶሎ ሄጄ አቦል ድራፍት ፉት ለማለትም (ሆ የድራፍትም አቦል አለው እንዴ) እየሮጥኩ ገባሁ ታዲያ ገና ከመግባቴ ዘወር ስል ምን ባይ ጥሩ ነው ? አለም ዘጠኝን ፡፡ አለም ዘጠኝ ማለት ወይኖ ናት ወይኖ ማለት እንደገና ወደ ትክክለኛው መዳረሻ ስም ስናቀና ወይናለም ማለት ነው፡፡ አለም ዘጠኝ እምትላት ታዲያ አርጊቷ አክስቴ ናት ፡ ያ መንገደኛ ገትሮ የሚያስቀረው ፡ ያ የሹፌርን አቅል አስቶ በደንብ እንዳይዘውር የሚያደርገው ፡ ያ በላይዋ ላይ ሲሽከረከር የብቻው ነፍስ ያለው እሚመስለው መቀመጫዋ ነው እንግዲህ አክስቴን አለም ዘጠኝ እንድትላት የገፋፋት ፣ ሁሌም ስታያት ‹‹ አንቺ ወንድሜ ሞልቶልሻል በደህና ቀን ይኸን እቃ ሰጥቶሽ›› ‹‹ አለም ዘጠኝ ሆኖልሻል ምናለብሽ›› ‹‹አለም ዘጠኝ ፡ እረ አለም ዘጠኝ….›› እያለች ነው እምትጠራት፡፡
እና ምናብ ሆቴል ደርሼ እንደተገተርኩ ዘወር ስል ያጋጠመችኝ አለም ዘጠኝ ወይንም ወይኖ ናት ፡ ክው ነው ያልኩት ለምን እዚህ ስገባ አየችኝ ሳይሆን እንዴት እኔን ፈልጋ መጣች ነው ያስደነገጠኝ ‹‹እዚህ ለመግባት እንዲህ ትሮጣለህ ፡ ገርመኸኝ እኮ ነው የተከተልኩህ›› አለችኝ ፡ እኔም ከግርታዬ ለመውጣት ብዬ የሆነ ነገር ቀባጠርኩ ፡ እኔም እንደሚገርምሽ አውቄ እኮ ነው የሮጥኩት ወይኖ አልኳት ፡ ‹‹ተው እንጂ አይተኸኝ ነበር እንዴ ባካባቢው›› እረ አላየሁሽም ያው ምን ሰፈርሽ አይደል እንዴ ከሰፈርሽ አትጠፊም ከጎዳናውም ጭር አትይም ብዬ በመገመት ነው ምናምን ብዬ ቀበጣጠርኩ፡፡
ይበርዳል አይደል ነይ እስቲ ትኩስ ነገር ልልቀቅብሽ ብዬ አጄን ትከሻዋ ላይ ጣል አድርጌ የሆነ ጥግ ላይ ሄደን ተቀመጥን፡፡ ‹‹እሺ እንዴት ነው ተሰየምሽ ጃል?›› አለኝ አስተናጋጁ የምን ልታዘዝህ ፊቱን ወደኔ ጥሎ፡ ‹‹ዛሬ ደሞ አጀብ ብለሽ በዛ ብለሽ ነው የመጣሽው ልበል›› አለ ፡እንዴ እያየ አይደለ እንዴ ምን ልበል ይለኛል ያሰበውን ዝም ብሎ አይልም ምን አይነት ሰው ነው ፡ ደሞኮ ብሎታል በቃ ምኑን ነው ምን ቀረውና ልበል ምናምን ብሎ እሚቀባጥረው አልቀረብህም ፎግረህ ልብህ ውልቅ ብሏል አልኩ በውስጤ፡፡
እሺ ለኔ የተለመደውን አምጣልኝ ከዛ ተናግሬ ሳልጨርስ እራሱ ወዲያው አንገቱን ቀለሰና ‹‹አንቺስ ቆንጆ ምን ይምጣልሽ?›› አላት ‹‹ ወይን ይምጣልኝ›› አለች በሙሉ አፏ ፡ ከዛ ከመቅፅበት አስተናጋጁም ተሰወረ እኔም እጄን ኪሴ ሰደድኩ ፡ የልምድ ጉዳይ ሁኖ እጄን ብቻ በመስደድ ብሩን ሳላወጣ መቁጠር እችላለሁ፡ አስር ብር ፣ አንድ ብር ፣ ሀማሳና መቶውን ሁላ በድምፅ እለያቸዋለሁ ፡ ታዲያ እጄን ሰድጄ ቆጠርኩ አሰይ ተመስገን አልኩ ቢያንስ 580 ብር አለኝ፡፡ ግን እሷ ምን ነካት ፡ እኔ ትኩስ ነገር እንጠጣ ብዬ ነው ያስቀመጥኳት ፡ ዘላ ወይን አምጣልኝ ሆ እውነትም አለም ዘጠኝ አልኩ በውስጤ አክስቴ በምትጠራት ስም፣
እሺ ወይኖ ቀሽት
‹‹እሺ አጅሬው›› አለችኝ ስሜን እንደማታውቀው ፡ አጅሬው ነው እሚሉኝ ሰፈር ውስጥ ታዲያ እኔም ለምጄው አጅሬውን እንደስም ከቆጠርኩት ሰነባበትኩ እንደውም በስሜ ሲጠሩኝ መደንገጥ ጀምሪያለሁ በቃ አጅሬው ተመችቶኛል ፡ ለምን አጅሬው እንዳሉኝ ግን ጠይቄ አላቅም ፡ አንዳንዱ ሁኔታዬንና የምናብ ሆቴል ጀብደኛነቴን አይቶ ነው አጅሬው የሚለኝ አብዝሀኛው ሰው ግን ስሜ እየመሰለው ነው ‹‹ደህና አደርክ አጅሬው ፣ አክስትህስ ደህና ሰነበቱ አጅሬው ፣ ስራ ጥሩ ነው አጅሬው›› ብሎኝ እሚያልፈው፡፡
ወይኑ ከች አለ ፡ ያን አለንጋ ጣቷን በጠርሙሱ አንገት ላይ ያረፈውን እጇን በተመስጦ ሜታዬን እየተጎነጨው ማየት ጀመርኩ ፣ ከኮካ ጋር ቀላቅላ ወይኑን አየሁት ፡ የሷን ፊት አየሁት ፣ ቡቱ የተቀባውን የግርግዳ ቀለም አየሁት ፣ ምን አይነት ወይናማ ቀን ነው አልኩኝ ፣ በምናብ ተሰደድኩ እውነትም ምናብ ሆቴል አልኩ ገና ሁለት ሱስቴ እንኳን ሳልጎነጭ ምሰጣዬ ከቀጠለበት ያ ቀዥቃዣ አስተናጋጅ ዛሬ መቸም ያለወትሮው ተንቀዥቅዧል መጣና ‹‹እ እናቱ መቀመጫ ልጨምርልሽ?›› አላት ፡ ክው ነው ያልኩት ፡ ሊያልቅ የሚችለው ነገር ቢያንስ እምትጎነጨው መጠጥ ነው ፣ ወንበር አያልቅ እንዴት ልጨምር ይላል ብዬ ወደ ታች ወደተቀመጠችበት መቀመጫ አይኔን ወረወሩኩ ፣ ለካ እዛ ቤት ውስጥ ያለው ተስተናጋጅ ሁሉ አይኑ ከገባን ጀምሮ የወይኖ መቀመጫ ላይ ነው የከተመው ፣ ለካ የወይኖም መቀመጫ ያረፈበት የሆቴሉ መንበር አልበቃው ብሎ ዳርና ዳር ተንከርፍፏል ፣ እናም ‹‹ፊት ለፊት ቆሞ ሲከታተል የነበረው የሆቴሉ አስተዳዳሪ ነው የላከኝ›› አለኝ አስተናጋጁ ፣ ለምንድን ነው የላከህ ‹‹በቃ እዛ ሆነው ብታየው እኮ ወንበሩ ያሳዝንሀል በጣም አጨናንቃዋለች ቆኒጂት›› እና ብሎ ቀጠለ ‹‹ሂድ ወንበር ትቀይር ወይ እሱ ይቀፋት ፣ እኛ ወንበሩን እንፈልገዋለን በላቸው ስላለኝ ነው ይቅርታ ›› አለ ጨዋ መሳይ አንገቱን ቁልቁል ቀልሶ……..

…….ክፍል ሁለት….ይቀጥላል 

No comments:

Post a Comment