Thursday, December 12, 2013

ሲገናኝ
…………..
በካሌብ(ስንታየሁ)አለማየሁ

’’ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው’’ ይባል የለ ፣ ጓደኞቼም እንዲሁ አስተኔ ህይወት ገጥሟቸዋል፣ ማለትም ፣ አንደኛው ሲጋራ ፋብሪካ ፣ አንዱ አረቄ ፋብሪካ እንዲሁም ሌላኛው ደግሞ ሆቴል ውስጥ ስራ ተቀጥረዋል፡፡ ታዲያ ’’ስራ ለሰሪው እሾህ ላጣሪው’’ እንድል ያስባለኝ ነገር ቢኖር ፣ ሲጋራ ፋብሪካ የተቀጠረው ጓደኛዬ እጅግ ሲበዛ የሲጋራ ሱስ ያለበት ፣ ገና ፊቱን ሲያዩ የሆነ የሱስ ኩይሳ ያለበት እሚመስል ሰው ነው ፣ አጅሬው እና ሲጋራ ዳግም ተገናኙ ዋው ፣ እንደተቀጠረ ደወለልኝና ‹‹ እልልል…..ጓደኛዬ ደስ ይበልህ ደስ ብሎኛል አለኝ›› እንዴት ነው አሪፍ ደመወዝ አለው እንዴ ? ስለው ‹‹ እንዴ እረ ከደሙዙ በላይ ጥቅማጥቅሙ ነው ጮቤ ያስረገጠኝ ጀለሴ›› ምን ተገኘ ደሞ? አልኩ ተረጋግቼ ‹‹ በወር እያንዳንዱ ሰው አራት አራት ፓኬት ሲጋራ በነፃ ይሰጠዋል ፣ ነገር ግን እኔ ደግሞ ሀላፊ ስለምሆን ለኔ ሰባት ፓኬት ተፈቅዶልኛል እና ይሄ አያስደስትም ›› አለኝ እየተፍለቀለቀ ፣ …..አሰብኩት ይህ ሰው መቸም ማጨስ እስካላቆመ ድረስ እና ለዚህ ለማይረባ ነገር በየቀኑ ገንዘቡን ከሚከሰክስ ፣ ባይሆን በነፃ ማግኘቱ ጥሩ ነው ፣ እሱ እንኳን ደስ ያለን ብሎ ሲነግረኝ ነገር ግን እኔ በጣም አዘንኩ ፣ ሞቻለሁ ብሎ የነገረኝ ነው የመሰለኝ ፣ አጠገቤ በረኪና አስቀምጨ ልጠጣው ነው ያለኝ ነው የመሰለኝ ፣ አስቡት እስቲ ገንዘብ በሌላው ሰአት አንድ ፓኬት በቀን የሚምግ ጀግና አሁን ሰባት ሰጥተውት ጭራሽ ቶሎ ሙትልን ፣ ወግድልን አንይህ ይመስላል እኮ ጎበዝ….አራዳ ጉራጌ ቢሆን ኖሮ በየወሩ የሚያገኛትን ሲጃራ አትርፎ ይነግድባት ነበር….ለማንኛውም ግን ለሱሰኛም አምላክ አለውና ስራ ሰሪው ወይንም ደግሞ ጭስ እና አጫሹ ተገናኝተዋል፡፡
‹‹አረቄ ፋብሪካ ምን እንደሚገጨን ታውቂያለሽ ?›› አለኝ ይሄኛው ሞዛዛ ጓደኛዬ ደግሞ በቁሙ የአረቄ ቦይ ታውቃላችሁ እንደዛ ሆኗል፡፡ በቃ ጠዋት ተነስቶ እሷን ፉት ካላለ አይነቃም ፣ ባገኛት አጋጣሚ ሁሉ በቃ መለጋት ፣ መለጋት ነው ስራው ደሞ እኮ ወገኞች ያ ሲጋራ እሚምገውና ይቺ አረቂ ፉት እምትለው ጀለሴ ሲፎጋገሩ ! ፣ የሆነ ቀን ይቺ ፉት እምትለዋ ጭስ ነገር አልወድም ምናምን ብላ የሷ አረቄ ግን ቅዱስ ተግባር እንደሆነ እምትቆጥረው ፣ የሆነ ሳይኖራት ተበድራ ተጠቃቅማ ምናምን ቀብረር ነገር እምትለዋ ፣ ቀንዳም ሱሳሟ ጓደኛዬ ባይ ዘ ወይ ያው እንደኔ አጭር ቀጭን ስለሆነች ነው አንቺ እያልን በሴት ስም የምንጠራት እንጂ ከወንድም ወንድ ናት ሌላው ሌላው ላይ ማለቴ ነው! ‹‹ ቆይ አንተ ለምን ሱስ አታቆምም ፣ አይደብርህም እንዴ ! እኛስ ይቺን ነገር ፉት ብንል ተፅፎልን ነው ! እንዴ እውነቴን እኮ ነው ፣ አቁም እስቲ አፍህን ምድጃ አታርገው በናትህ›› ምናምን ብላ ጀለሴ አጫሹ ላይ ጉራዋን አጨሰችበት ፣ አሀሀሀሀይ ወገኞች እረ አታስቁኝ አልሸሹም ዘወር አሉ ነገር እኮ ነው ጭውቴው ‹‹ቆይ ምን ተብሎ ነው ላንተ የተፃፈልህ ባክህ ፣ ማን ነው ደሞ የፃፈልህ ፣ የት ላይ ነው የተፃፈልህ ደግሞ ሆ?›› አላት ይቺን ጉረኛ ጓደኛዬን ፣ ታዲያ ሁለቱም በሙሉ ትጥቅ ሁነው ነው እንዲህ እሚነታረኩት ፣ በሙሉ ትጥቅ ስል ያው ቀጮም ከአረቂዋ ጋር ፣ እሱም ከሲጋራው ጋር ሆነው ነው ማለቴ ነው ካልገባችሁ፡፡ ከዛ ምን ብላ ብትመልስ ጥሩ ነው ይቺ ጉረኛ ፈላስፋ እሷ እሚሉ ፈላስፋ እና አንባቢ ደግሞ ኤዲያ….‹‹ ስማ ወይን ያስተፈስኪ ይለዋል አምላክ በቃሉ ፣ እና እኔ ደግሞ ወይን መግዛት ያልቻልኩት ፣ ፒን ያስተፈስኪ ብዬ አረቂዬን እጨልጣለሁሁሁ አሀሀሀሀሀ ፣ ሞኞ ›› ምናምን ብላ ሙድ ያዘችበት ፣ መፅሀፍ ቅዱስን ተሳፈጠች አይገልፀውም! ይቺ ቀጫጫ !.....
እናላችሁ ያው አረቄ ፋብሪካ ገጠመው ለዚህኛውም አረቂያም ጓደኛዬ! በቃ መቸስ እግዜር የከፈተውን ….አይደል ተረቱ….እግዜር ባያመጣውም ሱሱን ፣ ያው ለሱሰኛም ሱሰኛ መስሪያ ቤት ተፈጥሯል መሰለኝ ፣ እንደየፊናቸው እና እንደየተሰጧቸው በየመስሪያ ቤቱ ተሰገሰጉ ‹‹ ‹‹አረቄ ፋብሪካ ምን እንደሚገጨን ታውቂያለሽ ?›› አለኝ ፣ እረ አላውቅም ‹‹ በየወሩ ሉክ! በየወሩ እ…ስድስት ስድስት ጠርሙስ አረቄ ይገጨናል ፣ እኔ ደግሞ እ…ሀላፊ መሆኔን አስመልክቶ ከአንድ ቮድካ ጋር ዱቅ ይደረግልኛልልልል ፣ አሁን ያዝ ከእግዜር ውሀህ ጋር ችርስ አቦ!›› አለኝ በደስታ ፣ አሁንም እኔ ግን አዘንኩ ፣ ከነበራቸው ቀንድ ያወጣ ሱስ ላይ ጥቅማ ጥቅም ብሎ ይሄንን የመሰለ ሰይጣን ተግባር መፈፀም ፣ በቃ ሰርክ ሳገኛቸው ጓደኞቼን አጭሰው ከስለው ፣ ጠጥተው ሰክረው ፣ ሌሎቹማ ስንቶቹ ቤት ሰርተው ሰርተው ፣ አከራይተው አፈናጠው ምናምን እኚህ የኔዎቹ ፣ ሱሳቸው እንጂ ህልማቸው ላይ መፈናጠጥ አልቻሉም ፣ በቃ ስናወራ ብትሰሙ ህልማቸው ሌላ ፣ መዋያቸው ሌላ ….ፍየል ወዲያ …..ቅዝምዝም….ምናምን ብቻ በቃ …ለነገሩ እኔም ብሆን ህልሜን አልኖርኩም ግን ምንም ቢሆን በጣም በጥቂቱም ቢሆን ከነሱ እምሻለው ፣ ይቺኑ ጥቂት ህልም በአረቄ ምናምን አላጠብኳትም አሁንም አብራኝ አለች፡፡
የዚህኛው ሱስ ደግሞ ለየት ይላል ፣ የዚህን ሱስ እንኳን እኔም ቢይዘኝ የት በደረስኩ ያልኩበት ነበር ፣ የዚህኛው ጓደኛዬ ሱስ ምግብ ነው ታድሎ ነገር ግን ለዚህ አገር አይሆንም ምናምን እሚሉ የደሀ አመለካከቶችና ነቆራዎች ይደርሱታል ፣ ግን በልቶም ያስመሰክራል እኮ ፣ እኔ ፀጉሬን እያሻሸው ስወጣ ትዝ ይለኛል ገና ከህፃንነታችን እሱ ሁዱን እያሸ ነበር ብይ ለመጫወት እምንጠራራው ፣ በቃ የሆነ ሲያድግ እራሱ በደንብ እንዲበላ ይመስላል ፣ ከሌሎች ኢትዮጲያውያን ቤት በተለየ እነሱ ቤት ስለ ምግብ በደንብ ይተረት ነበር ፣ እነ ካንጀት ካዘኑ …….፣ እነ ሆድ ያባውን………፣ እነ ሲበሉ የላኩት ብቻ ምን አለፋቹ በቃ በሆድ ዙሪያ የተነገሩ ሁላ እነሱ ቤት ተፅፈዋል ፣ ሆዳም ሁላ!
እና ይሄ የሆድ አባት የእህል አፈንፋኝ ፣ አድሉ እያሸተተች ሄዳ ሆቴል እንዲቀጠር አደረገችው ፣ በቃ ከምንጩ ተጣደበት ነው ያሉት የሰፈር ሰው ሁላ ፣ ‹‹በስማም እንግዲህ በምግብ ሊጠመቅ ነው በሉኛ ›› አሉ እማማ እንትና አፋቸውን አጣመው ሆ ፣ እሱ ለጎረሰ የሳቸው አፍ ማጣመም እስቲ ምን ይባላል ፣ አይ አበሻ እንደው ፣ አስቂኝ ነገሮች ነን አንዳንዴ!
እና እንደፈረደብኝ ይሄም መጥቶ ስራ ሲቀጠር ነገረኝ ፣ እኔ ይኸው እነሱ ስራ ይቀጠራሉ ፣ ይቀጠራሉ ፣ ሱሰኞቹ እንኳን ስራ አግኝተው እኔ በቃ ይሄው ቁጭ ብዬ እነሱን መምከር ሆኗል ስራዬ ፣ አንድ ቀን ግን የጤነኞችም አምላክ ፣ ለኔም ያሽረኝ ይሆናል፡፡ እና ያው እንዳልኳችሁ የዚህኛው ጥቅማጥቅም ደግሞ በቃ መብላት ነው ‹‹ ቁርስም ፣ ምሳም ፣ እራትም የሚችል ሆቴል አይተህ ታቃለህ? ለነገሩ አንተ እንዴት ታያለህ ፣ የተማርከው መረጃ ምናምን ምግብ በዞረበት እማይዞር ፣ እየውልሽ እኔ የሆዴ አምላክ ፣ ስንት ሺኅ ክትፎ በሚዛቅበት ፣ ስንት ሺኅ በቃ የምግብ አይነት በሚፈተትበት ማህሌት ውስጥ እኑር አረገኝ ፈጣሪ እና ያመጣልኝን እየበላሁ መኖር ነዋ›› አለኝ ፣ እኔ እንዲያ ሲነግረኝ እራሱ ገና ማስታወቂያ ሳይ ውዬ አረፍ ማለቴ ነበር ምሳ እንኳን አልበላሁም ፣ ተመልከቱ እስቲ ታዲያ በይ እና ተበይ ፣ ጭስ እና አጫሽ ፣ መጠጥ እና ጠጪ ሲገናኙ ስራ ለሰሪው አያሰኝም ….ምናለበት እንዲህ ሁላችንንም በምንፈልገው ቦታ ቢቀጥረን ….አይዟችሁ አይቀርም ፣ ግን ሱስን ወዲያ ፣ አስቡት እስቲ የሰው ልጅን ያህል ታላቅ አሳቢና አገናዛቢ ፍጥረት ፣የምን በሆነ ግኡዝ ነገር ፣ሱስ ተይዞ መጠፍነግ ነው ፣ እረ ላሽ!

No comments:

Post a Comment