Friday, July 18, 2014

የክብር ማዕረግ

የክብር ማዕረግ
……….

ለኢኮኖሚስት ገብረህይወት ባይከዳኝ ፣ ለአርቲስት (ፋዘር) ተስፋየ አበበ ፣ ለድምፃዊት አስቴር አወቀ እና ለአትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የክብር ዶክትሬት ተሰጥቷቸዋል፡፡ ለኛ የሰሩልን የኛን ሰዎች ከዚህም በላይ ብናከብራቸው ምንኛ ደስ ባለኝ ፣ በተለይ ደግሞ በህይወት እያሉ ይህን ክብር መስጠት ባለሙያዎቹ አገራቸውን፣ ዜጋቸውን እና ሙያቸውን የበለጠ እንዲወዱ እና በሰሩት መልካም ስራ እንዲኮሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ነገር ግን ትንሽ የክብር ዶክትሬቱ አሰጣጥ ላይ የሆነ ነገር ብል ደስ ይለኛል፡፡
ለምንድን ነው አስቴርን ጎንደር ዩንቨርስቲ የሰጣት?
ለምንድን ነው ገ/ህይወት ባይከዳኝን መቀሌ ዩንቨርስቲ የሰጠው?
ለምንድን ነው ለጥሩነሽ ዲባባ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ የሰጠው?
አስቴር የዘፈነችው ስለ እያንዳንዳችን ፍቅር ነው ፣ ባህል ነው ፣ ሀሳብ ነው ፣ ለጎንደር የዘፈነችው ዘፈን አለ ፣ በጉራግኛ የተጫወተችው ዘፈን አለ ብቻ ምን አለፋቹ አስቴር በሙያዋ አንቱ የተባለች ምርጥ ድምጻዊት ናት ታዲያ ጎንደር ስለተወለደች እና ጎንደሬ ስለሆነች ነው ጎንደር የሚሰጣት? ቆይ እኔ እምለው የያሬድ ሙዚቃ ት.ቤት ምንድን ነው ስራው? የሀገሪቱ ታላቅና አንጋፋ የዚህ ዘርፍ ባለቤት ነው ስለዚህም በኔ እምነት እያንዳንዱ  ስራ ሲሰራ በዘርፍ ሲሆን ደስ ይላል፣ አስቴር በያሬድ ት/ቤት ላታልፍ ትችላለች ነገር ግን ይህ ሀገራዊ የሙዚቃ ተቋም ሀገራዊ ሙዚቀኞችን ቢሸልም እሚያምርበት እሱ ነው፡ ያሬድ ት/ቤት ዶክትሬት መስጠት የለበትም ቢባል እንኳን የሀገሪቱ ትልቁና አንጋፋው የመጀመሪያው ዩንቨርስቲ አ.አ.ዩ ነው መስጠት ያለበት ባይ ነኝ ዘሎ እንደው ሁሉን በክልል ማሰብ ቢቀርብን መልካም ነው ጎበዝ፡፡
የገ/ህይወት ባይከዳኝም ጉዳይ እንዲሁ ነው መሆን ያለበትትትትት…..ለምንድን ነው በግድ በክልል እምንጠርፋቸው ? እሳቸው ምርጥ የኢትዮጲያ አይደሉም የአፍሪካ ኢኮኖሚስት ነበሩ ፣ ማንም ፈረንጅ የሚቀናባቸው ጭንቅላት የነበራቸው ሰው ነበሩ ፣ እሳቸው ምርጥ የኢትዮጲያ ልጅ ናቸው እሳቸውን የመሰለ ሰው ዶክትሬት ቢደራረብ ልዩነት የለዉም እንጂ ሁሉም ዩንቨርስቲ አንድ አንድ ዶክትሬት ቢሰጧቸውም አንቀየምም ነገር የሀገሪቱን ምርጥ እኮኖሚስት የሀገሪቱ አንጋፋውና ትልቁ ዩንቨርስቲ አሁንም አ.አ.ዩ ነው መስጠት ያለበት መቀሌ ከፈለገ ሌላ ማዕረግ ይስጣቸው እንጂ መጀመሪያ በሀገር ደረጃ እናስብ ሮጠን በትውልድና በሀረግ በክልል ምናምን እነሱ እኮ ሲሰሩ እውቀታቸውን ለመቀሌ ፣ ለጎንደር ለባሌ እያሉ አልከፈሉም እንደ ኢትዮጲያዊነት ነው የኖሩት እኛም ታዲያ እንደ ኢትዮጲያዊነት ልንሸልማቸው ይገባል፡፡
ሌላው እና በጣም የገረመኝ ነገር ለጥሩነሽ ዲባባ በመጀመሪያ እራሱ ዶክትሬት መሰጠቱ ትንሽ የቸኮልን መስሎኛል ፣ እንዲህ ስል እምትበሳጩ ትኖራላቹ እኔ ምናገባኝ እኔ የኔን ነው እምናገረው እናንተ የናንተ ስላላችሁ የናንተንም አውጉ፡፡ ገና ሀያ ቤት ላለች ወጣት ከአቅሟ በላይ ሰርታ ብታኮራንም ቅሉ ትንሽ መቆየት የነበረብን ይመስለኛል ፣ ዶክትሬት ካልሰጠናት ለሌላ አገር ትሮጣለች ተብሎ ተፈርቶ እንደሆነ አላቅም፡፡ ቢያንስ ሀይሌ ዶክትሬቱን በሰጠንበት እድሜ ፣ ቢያንስ ለደራርቱ ቱሉ ዶክትሬት በሰጠንበት እድሜ እስክትደርስ ብንጠብቃት መልካም ነበር ፡፡

በመሰረቱ እኔ እሚገባኝ እስከዛሬ ሰዎች ትልቅ ከሆኑና አቅማቸው በመዳከም ሁኔታ ላይ ሲገኝ ነው ዶክትሩት የሚሰጠው እንደዛ ስል ግን ለእነ ሀዲስ አለማየሁ እና ከበደ ሚካኤል የተሰጠው አይነት በጣም ከረፈደ አይነቱን እየደከፍኩኝ አይደለም፡፡ ጥሩዬ ገና ልጅ ናት ቀስ ብሎ ሊደርስ ይችላል ባይ ነኝ በተጨማሪም ተስፋ እያደረገችም ብዙ እንድትሰራ ያስችላት ነበር ትን ቢዘገይ ምንም እንኳን አሁንም እንደማትሰንፍ ቢገባኝም፡፡ሌላው ጉዳይ አሁንም ዘርፉን የወከለ ኢትዮጲያዊ ባለቤትነት ጉዳይ ነው ፡ ለመሆኑ ቆይ ሀገሪቱ ውስጥ የአትሌቲክስ ት/ቤት ወይንም የት.ምርት ክፍል የለም እንዴ? በአትሌት ዘርፍ እርግጠኛ ባልሆንም ኮተቤ ያለው ይመስለኛል ካለ ታዲያ ምን አገባውና ነው አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ዶክትሬት የሚሰጠው? ነው ወይስ እሷ አዲስ አበባ ስላደገች ይሄም በክልል መሆኑ ነው? በክልልማ ስለሆነ ነው ለደራርቱም ጂማ ዩንቨርስቲ የሰጣት እንጂ ሁሉስ አንድ ዘርፍ አልነበሩምን? እኔ እንዲህ ባይሆን ጥሩ ነው ባይ ነኝ ኢትዮጲያኖችን ስናከብር እንደ እትዮጲያ ቢሆን ደስ ይለኛል….

No comments:

Post a Comment