Wednesday, November 6, 2013

አለቃና ጭፍራ

አለቃና ጭፍራ

ካሌብ(ስንታየሁ) አለማየሁ

አይ አኛ ቅጥረኞች ፣ አስራ ምናምን አመት ተምረን ዲግሪ ምናምን በጥሰን ስናበቃ ስንት የበጣጠሰ ጭንቅላታችንን ለሆነ ግለሰብ መስሪያ ቤት የ30 ቀን ወያላነት መቅጠራችን ሳያንስ አሁን አሁንማ ጭራሽ ማንነታችንን ሁሉ ነው እኮ ለቅጥረኛነት አሳልፈን የሰጠነው ፣ ይሄን ልል የቻልኩት አለምክኒያት አይደለም፣ ባጠገቤ ብዙ የማውቃቸው ሰዎች ከዱሮ ባሪያ ንግድ ባልተናነሰ ለቀጣሪ ባለሀብታቸው ሲሽቆጠቆጡ አያለሁ፡፡ በቅርብ የማውቀው እና ለወትሮው በራስ መተማመኑ ከፍተኛ የነበረ አንድ ጓደኛየ በቀደም ለት፣ እሱ ቢሮ ሄጄ እያወጋሁ ሳለ፣ የድርጅቱ ባለቤትና የጓደኛየ አለቃ ያው የተለመደ ሱፉን ገጭ አርጎ ፣ በከረባት ታንቆ ፣ ያው የተለመደ የባለሀብትነት ምልክቷን የመኪና ቁልፍ በጁ ይዞ ወዲያና ወዲህ እያቅጨለጨለ ፣ የጓደኛዬን ቢሮ አንኳኳ ፣ እኔ ቀድሜ በመስታወት ውስጥ ተሸግሬ አመጣጡን አይቼ ነበር ፣ ኮራ ቀብረር ማለት ያበዛል ፣ ፊቱን አይተው ደሀ እንደሚንቅ የሚያስታውቅበት ሰው ነው ፣ በሩን አንኳኳ እንጂ እስክንከፍትለት አልጠበቀም እራሱ በርግዶት ገባ ፣ ታዲያ ያኔ የኔው ጉደኛ ጓደኛ ምን ቢል ጥሩ ነው? ‹‹ ወይኔ ጉዴ ብዙ ሰአት አንኳኩ እንዴ ጌታዬ! ፣ አልሰማዎትም ነበር እኮ ፣ ለምን ያንኳኳሉ ቆይ ፣ ለመሆኑ እስቲ እጣዎት ያንኳኩበት አላመመዎትም ይሆን? ›› ብሎ እጣታቸውን ለጥ ብሎ ማሻሸት ሲጀምር ፣ በቃ ያኔ የት እንዳለሁ አላቅም ፣ የኔ ጓደኛ ስለመሆኑም ተጠራጠርኩ ፣ ኢትዮጲያዊ ስለመሆኑም አሰብኩ ፣ ‹‹እንዲህ አይነት መሽቆጥቆጥ በዘራችን የለም›› ይል ነበር አያቴ ፣ እኔ ግን እምለው እንደውም ‹‹ እንዲህ አይነት መሽቆጥቆጥ ባገራችን የለም›› ነው ፣ እንዲያ ቢሆንማ አበሻ በቅኝ ግዛት በተቀፈደደ ነበር፡፡ አረ ጎበዝ ፣ ከልክ ያለፈ ማጨብጨብስ የሆነ የዱሮ ባሪያ ስታይል ነው!
‹‹ ማነው ደሞ ይሄ ከየት የመጣ ነው?›› አሉ የሱ ጌታ ፣ እ….ብሎ እየተንቀጠቀጠ ጀመረ ‹‹ እ….ጓደኛየ ነው ፣ ሊጠይቀኝ መጥቶ ነው ጌታየ›› አላቸው አይናቸውን እንኳን ቀና ብሎ ሳያይ..‹‹ እንዲህ ነችና ›› ብለው ማጓራት ጀመሩ ‹‹ እና በስራ ሰአት ነው መጥቶ የሚጠይቅህ አንተ?›› ቀጠሉ ‹‹ የኔ ቢሮ ከጓደኛህ ጋር መቀጣጠሪያ ቡና ቤት አረከው አንተ? ››
አልቻልኩም በቃ እንዲህ ሲሉ መስማት ግን አልቻልኩም ልናገር ወሰንኩ ፣ ቢፈልጉ በኔ ሰበብ ያባሩት የእውነት አምላክ ያቅለታል አልኩና ‹‹ ሄይ ሄይ አንዴ ›› ብየ ድንፋታቸውን በማቋረጥ ጀመርኩ ፣ እሱ እኮ እንኳን ሄይ ሄይ ብሎ ሊናገራቸው ቀርቶ ሀይ እንኳን አይላቸውም ፣ ይልቁንም በረጅሙ ፣ ‹‹ እንደምን አደሩ ጌታየ ፣ እርሶን ያኑርልን ፣ እኛን ደግሞ ጠንካራ ሰራተኛ አድርጎ ፣ ድርጅቶን ትርፋማ ያድርግልን ›› በስማም ሎምን አይቀርም ጎበዝ በልክ ነው እንጂ…
እና እኔ በንዴት ንግግሬን ቀጠልኩ ‹‹ እየውሎት ፣ በደንብ ይስሙኝ እሺ ፣ ልጁን እውቀቱን እና ጭንቅላቱን እንጂ የቀጠሩት ፣ ሁለመናውን አሳልፎ የሚሰጥዎት ባሪያዎ እንዲሆን አይደለም ፣ ምናልባት ይሄ አይነት አመለካከት በዱሮ ጊዜ ይሰራ ይሆናል ፣ ያውም ሌሎች አፍሪካ ሀገሮች እንጂ ፣ ኢትዮጲያ ውስጥ I think እርሶ የመጀመሪያው ባላባት ጓደኛዬ ደግሞ የመጀመሪያው ባሪያ ሳትሆኑ አትቀሩም ›› ቀጠልኩ እረ አልበቃኝም ‹‹ እርሶ እንዳሉት ደግሞ ፣ ቡና ቤት መሰለህ እንዴ የኔ ቢሮ ላሉት ፣ እኔ እና እሱ ቡና ቤት ተቃጥረን አናውቅም ›› ብዬ ልቀጥል ስል አቋረጡኝና ‹‹ ምን በምናቹ ትጠጡታላችሁ ፣ ብር ስለሌላቹ ነዋ ፣ ቡና ዝም ተብሎ እንደ ውሀ ተለምኖ እሚጠጣ መሰለህ እንዴ ›› አሉኝ ..ያኔ በጣም ተናደድኩ ፣ በጠዋት እስቲ ከሰው ጌታ ጋር እዚህ ምን እግር ጥሎኝ ነው ….ቀጠልኩ በንዴት ‹‹ ትሰማኛለህ አንተ ሰውዬ›› በጣም ስሌበሳጨው ሳይታወቀኝ ከአንቱታ ወደ አንተ ወረድኩ ፣ ያኔ ጓደኛዬ ምን ውስጥ ይግባ ወይ ዝም በሉ ብሎ መናገር አይችል ፣ ወይ መብቱን አያስከብር ፣ ዝም ብሎ እኔን አይን አይን ያየኛል ፣ ይሄኔ እኮ መቸም ካሁን በኋላ እዚህ ስራ አያስቀጥሉኝም ፣ ይሄ ሰይጣን የሆነ ልጅ በምን ቀን ነው የተዋወኩት ፣ ካባረሩኝ እስቲ የት ልሰራ ነው ፣ እያለ በውስጡ እያሰላሰለ ይሆናል ፣ በራስ መተማመኑን ሰውየው ስለነጠቁት ሌላም ቦታ ቢቀጠር ያው እንደሚሆን ሳስበው እኔም አሳዘነኝ ፣ ግን ሰውየውን ልክ ልክ መንገር አለብኝ ብዬ ቀጠልኩ ፣ እረ እንኳንም አንተ አልኳቸው ፣ ዱሮም ለማይገባቸው ሰው ነው አንቱ ብዬ የጀመርኩት ፣ እዛ ላይ ደግሞ አስቡት እስቲ አንቱ ብሎ መሳደብም ፣ እንደው ለጠብም አይመችም እኮ አንቱታ!
‹‹ እየውልህ ትሰማኛለህ አንተ ሰውዬ ፣ እኔ ጓደኛዬ ትልቅ የተከበረ ቢሮ ውስጥ ነው ፣ ድርጅት ውስጥ ነው እሚሰራው ብዬ ነው የመጣሁት ፣ ደግሞም ማንም ሰው ጓደኛውን እገረ መንገዱን ሲያልፍ እሚሰራበት ቦታ ሄዶ ቢጠይቀው ምንድን ነው ችግሩ ፣ ደግሞ እኮ እየሰራ ሊያዋራኝ ይችላል ፣ ስራው ባፍ እሚታኘክ ነገር አይደለም አይደል? ምን አይነት አገዛዝ ነው ባክህ እምትገዛው ፣ አታፍርም እንዴ በዚህ ዘመን ፣ እንደጊዜው ኑር እንጂ ፣ አንተ ሀብት ቢኖርህ እንደኛ አይነቱን ጭንቅላት ካላገኘህ ብር ብቻውን ምንም አይሰራም ፣ ስለዚህ በምንህም ልትንቀባረር እና ›› ልበለው አልበለው ብዬ ‹‹ ልታናፋ አትችልም እሺ….›› 㙀ልኩጽ በድፍረት ምን ያመጣል ቢያባረው እሱን እንጂ ከኔ ላይ ድርሽ አይልም …..ለጥቂት ደቂቃ ዝምታ ሆነ ፣ ፀጥታ በዚያች ቢሮ ነገሰ ፣ በኋላ ሰውየው ተነፈሱ ‹‹ እ…..ጥሩ ተናጋሪ ነህ ልበል ›› ሲያመሰግኑኝ ግዜ አንቱታቸውን መለስኩላቸው እና ‹‹ ይበሉ›› አልኳቸው ፣ ጭራሽ እኔን አስፈቅደው ማወራት መጀመራቸውን ሲያይ ጓደኛዬ ምን ውስጥ ይግባ በራሱ አፈረ ፣ እ…. ብለው በረጅሙ ተንፍሰው ቀጠሉ ፣ ‹‹ እየውልህ እኔ ማንንም ሰው የመግዛት ፣ እንደ ባሪያም የማየት ልምድ የለኝም ፣ ምንም እንኳን እድሜ ከፍ ቢልም ፣ የዘመኑን አኗኗርና ፍላጎትም ጭምር አውቀዋለሁ u know ፣ ነገር ግን አንዳንድ ግዜ ሰዎችን ወደማይፈልጉትና ፈፅሞም ተመኝተውትና አስበውት ወደ ማያውቁት አለም የሚመሯቸው እራሳቸው ሰዎች ናቸው ፣ አየህ ይሄ ጓደኛህ ዲግሪ ለመያዙም እጠራጠራለሁ ፣ በራሱ ቢተማመን ኑሮ ፣ እራሱን እንደ ባሪያ ባልገበረ እና እኔንም እንደ ጌታ ባልቆጠረ ነበር ፣ ስለዚህ እማላውቀውን ባሪያ ሆኖ እንም ሆኜ እማላውቀውን ጌታ እንድሆን ያደረገኝ እሱ ጭባ ጓደኛህ ነው ፣ አሀሀሀሀሀ ›› ብለው በረጅሙ እኔን እና እሱን እያስተያዩ ሳቁ ፣ ‹‹ እና እኔ ነኝ ወይስ እሱ ጥፋተኛው ጃል? Anyways try to advice him not to act like this ›› ብለውኝ ቢሮውን ጥለው ወጡ ፣ ሰውዬው በጣም ታላቅ ንግግርን ተናግረዋል ፣ እኔ እንኳን ብዙ ግንፍል ግንፍል እያልኩ ለተናገርኩት ፣ ከቁብ ሳይቆጥሩኝ መልስ አልሰጡኝም ፣ ታላቅ ናቸው ፣ በስተት አንተ አልኳው ፣ የንዴት አምላክ ይቅር የበለኝ እንግዲህ….እራሳችንን አሳልፈን ካልሰጠን በቀር ሰዎች እኛን ለመቆጣጠርና ለመግዛት አይፈቅዱም ፣ አኛው በር ከሰጠናቸው ደግሞ ማንም ይሉኝታ አያጠቃውም ፣ ማንም ይረማመድብናል እንጂ ….ስለዚህ ጎበዝ በሚገባው ልክ እንከባበር እንጂ አንሽቆጥቆጥ፡፡