Wednesday, April 3, 2013

kalebalem's poetry




(ወግ)


በስንታየሁ(ካሌብ)አለማየሁ


ዝም ባለ አፍ ዝንብ አይገባበትም
ካልተናገሩ ደጃዝማችነት አይገኝም
………
ቆይ የቱን ተረት ንቀን በየቱ እንኑር
ለየቱ አፍ ይከፈት ለየቱ ዝም ይባል
ምን ይሉት ተረት ነው ምን አይነት አባባል
ቆይ ማነው የፈጠረው ፈላጭ ፈቃጅን ቃል
…….
በኛ ባሁኑ አለም ስልጣን እንደው የለም
ቢያልፍም አይነካንም
በውል ማውራት ቀርቶ ብንጮህ አይሰማንም
…….
ይልቅ ልክ ናችሁ ዝንብ ነፍሳት በዝቷል
ክፍት ያለ አፍ ካየ ዘሎ ጥልቅ ይላል
…..
ከልካይ በበዛባት በዚች የጉድ አገር
ዝንብ በበዛበት በዚህ ጦሰኛ አለም
ከዝምታ ወዲያ ሌላ አማራጭ የለም
……
መቸም አያልቅብን ንጋትና ወራት
ወጉ ወሬና ቧልት
ሁሉን ቢናገሩት ሆድ ባዶ ይቀራል
እሚል ተረት አለን
ለክፉ ቀን እሚሆን
ቃሉ ቋንቋው ሲያጥረን
ሰው ማውራት ሲያስጠላን
ውስጥ ውስጡን ለብቻ
ማልጎምጎሙ ሲያምረን
የምናመልጥበት ለብቻ መሸሻ
ሀሳብን ማመስኪያ ትንፋሽ መከለሻ
…….
እና ካለመናገር
ደጃዝማችነትም ብቻ አይደል የሚቀር
እራሱ አለመናገር እንጂ
አለማሰብም ነው የሚቀር
የሚዘጋ የሚደርቅ ከምንጩ እንኳ እንዳይቀር፡፡
….ይሻላል በቃ ዝም ዝም
ዝንብም ምንም እንዳይገባ እንዳያርም፡፡




(በበኩሌ)


መውደድሽ በልቤ እልቆቢስ ነው ስልሽ
መቸም አታምኒኝም ወረት ነው ትያለሽ
ለኔ እኮ ልዩ ነሽ ኮኮቤ ነሽ ብልሽ
አስመሳይ ወገኛ ዋሾ ነህ ትያለሽ
እኔ አንቺን ከጠላሁ ልቤ ባፌ ይውጣ
አንጀቴም ይዘርገፍ ሁሉ እቃዬን ልጣ
ብዬም ብምልልሽ ይባሱን ጠረጠርሽ
የአሽሙር ቀንድ አበቀልሽ
….ግን ብትጠረጥሪም አውቃለው እሙን ነኝ
አንቺ ካላራቅሽኝ አንቺው ካልጠላሽኝ
ዝንት አለም ናፋቂሽ ሁሌም ወዳጅሽ ነኝ
….የረሳሽ ይረሳ የጠላሽ ይጠላ ብዬ እስከመራገም
ብዬ እስከመለፈፍ ጎዳና የወጣሁት ብእር የጨበጥኩት
ስንቴ ስድብ ጥፌ ስንተዜ ቀንቼ ከጠብ ጫፍ የቆምኩት
ስሜቴን ዘንግቼው በህዋስሽ የኖሩኩት
ስምሽን ታትሜ በስምሽ ወይ ያልኩት
ብወድሽ እኮ ነው ነፍሴ አንቺን ብትመርጥሽ
እንደዚህ ሺ ጊዜ መውደድ የምነግርሽ
………
እመኒኝም ብዬ ሰርክ አልጨቀጭቅሽ
መውደድ እሚሉት ቃል ፍቅር ብሎ ኪዳን
በደም ስርሽ ሲፀርስ ሲኖር ነው ሚገባሽ
ውደጂኝም ብዬ ሽምግልና አልክም
ሰው በማመላለስ በአስታርቁኝ አላምንም
ልብሽ ካኮረፈም በሸምጋይ አይድንም
ነገር ግን አውቃለው ጥርጣሬ ይሉት ቃል
ደምሽን በክሎ ዋግምት ሁኖ በቅሏል
እሱን ለማጥፋት ነው የኔ መስዋትነት
የኔ ካንቺ መዋል የኔ አንቺን መሰኘት
………..
እና እንደነገርኩሽ ያው እወድሻለሁ
ያው አንቺም ጠርጥሪ መጠርጠር ፀባይ ነው
ወደው የሚያመጡት ከውስጥ የሚያሰርፁት
ወደው እንዳስገቡት ሲያሰኝ የሚነቅሉት፡፡


በስንታየሁ(ካሌብ)አለማየሁ

(ኑሮ ካሉት……)


ቤት መስራት
መኪና መግዛት
ሚስት ማግባት
ኢንዱስትሪ ማቆም
ህንፃ ድንጋይ መምራት
ማስተርስና ዲግሪ ዶክተርና ፕሮ ተብሎ መጠራት
እሺ ከዛስ
እቺ ናት ኑሮ ያልናት?
የምንጣላባት የምንዋጋባት
የምንስቅባት ቀን የምንፈጥርባት?
……
ለራስ በራስ ኑሮ ለራሱ በሞተ
አፈር አይዳብርም ሳር አይለመልምም
ወንዝ ውሀ አያቁርም ዝናብ ጠብ አይልም
ህፃን ቁሞ አይሄድም እናት አትስቅም
ወጣት አይበረታም ተስፋን አይሰንቅም
ሽማግሌ አይኖርም ቅርስ አይቀመጥም
አገር ቁሞ አያቅም ሰውም ሰው አይሆንም
……..
የድንጋይ ካብ መትከል
ትልቅ ሰማይ ጠቀስ አላቸው ለመባል
የራስን ሽንፍላ ለመክተት ለመቅበር
ከእውነት በመጋረድ እራስን ለማወር
ሌላ የካብ አለም በድንጋይ መከለል
አጥር ብሎ ጠርቶ በአጥሩ መተማመን
ወገን ወይ እንዳይለን እኛም ወይ እንዳንል
ላለመሰማማት ላለመተዛዘን ላለመጠያየቅ ላለመተያየት
እንደ ማቱሳላ ኑሮ ኑሮ ኑሮ በራስ ለራስ ብቻ ጃጅቶ ለመሞት
እኮ ይቺ ናት ኑሮ
ኖርን የምንላት ፣ ምንኮፈስባት?
እኛ ብቻ አርቅቀን እኛው በወደድናት
ልክነቷን ከቶ ያላወዳደርናት ፣
በኛው አለም ሚዛን መርቀን የሾምናት
ሀይል የሚሰምርባት ሆድ ያነገስንበት
የእንስሳ አይነት ዑደት ሚመላለስባት
የውድድር አለም የእሽቅድምድም እያልን ዘዴ እየቀለስን
የበላ አካል ብቻ ሆዱን ያነገሰ የሚፈነጭባት
የዛገ ቃል ያለው ብረት የታጠቀ እውነት የሆነባት
እኮ እቺ ናት ኑሮ በጠራ ሰማይ ስር የምንኖርላት
ያላቅሚቲ ኑረን ፣ ሺ ሞት ምንሞትባት?



አልኸድበት ነገር
……….
በስንታየሁ(ካሌብ)አለማየሁ


በጎዳናው መሀል እየሄድኩ እንዳልሄድ ሀሳብ ተጠናውቶኝ
ግትር እላለሁኝ በማየው ላይ ሁሉ አይኔ እየቀረብኝ
የማያቸው ሁሉ ሰርክ እያስገረሙኝ
እያደነዘዙኝ
እያብሰለሰሉኝ
ም…..ስ……..ጥ እልና
ወይ መልስ አልሰጣቸው
ወይ ብር አልሰጣቸው
ወይም ጠጋ ብዬ ከወጠራቸው ጭንቅ አልካፈላቸው
እንደው ከንፈር ስመጥ
ዝም ብዬ ስመሰጥ
እየሄድኩ አልሄድም
ቀኔ ግን አይቆምም እኔን አይጠብቅም
……
ይኸው ነው እውነቴ
መግባቴ መውጣቴ
መንገድ አለኝ እያልኩ
አልኸድበት ነገር ሰርክ መዋተቴ፡፡

የምልህ የለኝም ብለህ አትመልሰኝ
ይሉኝታ አጥሮህ እንጂ ባህል አፍክን ቋጥሮት
ፊትህ ይናገራል ግንባርህ ያወራል አፍህ ቃል ባይነግረኝ


በስንታየሁ

(የሆነ ሀላፊ አላት)
……..

አንደዚህ ናት ህይወት
እንዲያ ሆነን ኑረን
በእንዲህ የተቀበልናት
እንዲህ የመሆን እዳ
ወይም የመሆን እጣ
ወዲህ የገፈተራት
ልክ ናት
ስህተት ናት
አንድ ናት
ብዙ ናት
ቀይ ናት
ጥቁር ናት
ብለን የማንላት
በምንሆነው ብቻ
እየተገረምን
እየተደሰትን
እያለቃቀስን
እየለማመንን
እየተሰጣጣን
አብረን እየበላን
አብረን እየሞትን
የሆነውን ብቻ ሆነን የምንኖር
የመሆን ግኝት ነን ሁኔታ የሚፈጥረን፡፡

(ምኞት)

በስንታየሁ(ካሌብ) አለማየሁ


ደፍሮ ለመናገር ወኔውን የሸጠው
ምስኪን ያገሬ ሰው
‹‹እውነቱን ተናግሮ ከመሸበት ማደር››
ይላል ይተርታል
ግና ያው ይላል ሰርክ ይደሰኩራል
እንጂ እውነት ተናግሮ
መሽቶበትም አያውቅ
ማደሪያም አላጣ ቤሮጎም ጠቦት አያውቅ
……
ለኔ ግን ሲመስለኝ ………አሁን ይሄ ተረት
ምኞት መቸም አያልቅ
ምናልባት አንድ ቀን የመናገር መብረቅ
ብልጭ ያለ እንደሆን
ብሎ የተነበየው ቀድሞ የተረተው
የመጪ አለም ትንቢት አስቀድሞ ቃል ነው
…..
የመተንፈስን አምድ ካገኘ ፀጋውን
ይናገር ይሆናል እምቅ ትኩስ ሀቁን
የየልብ የልቡን ህገ እግዚብሄር ቃሉን
ስጋን መደለሉን
ነፍስን መሸንገሉን
ፍራት መደረቡን
ምናልባት …..ም…ና…ል…ባ…ት
ምናልባት አንድ ቀን የተወው እንደሆን፡፡



በስንታየሁ


(ይኸው ነው………..)


አሁን በቀደም ለት ስራ ተወዳደርኩ
እኔን ጣሉኝና እንትናን ቀጠሩ
ከእንትና ጋር ሾርኒ ሙድ ቢጤ ቋጠሩ
አምና የእህቴ ልጅ ንግዷ ተዘጋባት
ሀላፊ ተብየው ከሷ ጋር መጋፈፍ እሷን ማሸት አምሮት
እናቴ ከጥዳት አባቴ ከአባት ጦር ከጥበቃ ስራው
ቀሩ ተባረሩ ከእንጀራ ታገዱ ትዳር ውሀ በላው
ሁሉም በየዘርፉ መዝረፍና መቅጣት
ነፍስን ድባቅ መምታት ስጋን ሸቀጥ ማውጣት
እግርን ስንክል አርጎ እጅን እግር ማድረግ
ሆኗል የኛ ኑሮ ሆኗል የኛ ቢሮ
ካለው ጋር መብረር ነው አንገት አቀርቅሮ
ሞራል በቁም ገድሎ ቅስምን አሳርሮ
ስናጣ በመስገድ ሲኖረን እንደ እቃ ሰውን በመነገድ
የሀቅ ውል ጠፍቶብን ህያው የእውነት መንገድ
ሰው ሲሉን ሰው ሳንሆን አቤት እንላለን
በስም ቅስም ብቻ በወል እንኖራለን፡፡



በስንታየሁ
........

(.....መክሸፍ እንደኔ....)


ከካፌ ደጃፍ ላይ
ሴት ቀጥሮ ሴት ማየት
አለ ክፉ ምትሀት
አይን ያመጣው ጉድለት
…..
አንችን ለመጠበቅ ካፌ ቁጭ ካልኩበት
መጣች እኩይ ቆንጆ ቀልብ የምትነሳ
ቀጠሮ አስረስታ ልብን አሸፍታ አይን የምታሳሳ
በሷ ቤት ጨዋ ናት…አቤት ድንቄም ጨዋ
አሷም ሰው ቀጥራለች
ግን እኔን ታያለች…
ግራ ቀኝ…ፊት ኋላ
በግብብዳ አይኗ ትቀላውጣለች
ግን ግን ሰው ቀጥራለች…
ሰውየው እስኪመጣ ሌላ ሰው ታያለች
……
አይ የፍቅር ወጉ ተረቱ ስሌቱ
ያስቃል ይገርማል በሰከንድ ሲፋቱ
አሁን እኔና እሷም ባለፍቅረኛሞች ነው የምንባለው?
ፍቅረኛሞቻችን አርፍደው እስኪመጡ ሰው የምንከጅለው
አሁን እኔና ይቺም…ይቺም አይነ በላ
ወዳጇ ሲመጣ
ወዳጄ ስትመጣ
ጣፋጨ ኬክየ የኔ ማር ወለላ
ታራራም ታራራም
እንል እኮ ይሆናል መቸም ወግ አያልቅም
መቸም መወሻሸት መቸም መከዳዳት
እንደ እውነት አይከብድም
….
እና እኔ ልንገርሽ ተይኝ አትቅጠሪኝ
ሲቀጥሩ አይቼ ቀጥሬ ሊያምርብኝ
ዕረ እዲያ….
መቸም ሰው ነኝና የፍጡር አይን ያለኝ
ቀጥረሽ ለዝሙት ጦስ ሀጥያት ከምትዶይኝ
ይቅርብኝ አልምጣ እቤቴ ነይብኝ፡፡

በስንታየሁ (kaleb)


(ጉድ ነን)


………እንዴት ግን ያስጠላል በጎዶሎ መኖር
እያነሱ ማደር
በቅርታ ማፈር
እንዴት ይደብራል ፍላጎትን መግደል
ከሰውነት ተርታ ደርሶ መንከባለል
ሀሳብን በቁሙ በእውኑ አፈር ማልበስ
አንደበትን ማሰር ለጨቋኝ መቅለስለስ
ለገዳይ ማፈንደድ ለጣረሞት ማንከስ
ለይሉኝታ መጣስ ለእጦት እጅ መንሳት
ምፀት ከንፈር መምጠጥ በባዶው ማጋሳት
እንዴት ዝግንን ይላል
እየተቀበሩ ነፍስ እየተቀሙ አለው ብሎ ማውራት
ተራ ሸቀጥ ሆኖ ሰውነት ተገፎም ግር እማይልበት
ከራስ ማንነት ጋር ከሀገር ወንዝ ልጅ ጋር
ቂም እየተጋሩ እየተኳረፉ በግድ ሰው ነኝ ማለት
ወገን አለኝ ማለት
ሀገር አለኝ ማለት
…….
ማለት ማለት ማለት
ማለት ማያልቅበት
ምን አይነት ኡደት ነው
ነፍስ አለን ኑሮ አለን
ወንዝ አለን ሰው አለን
እያልን በእጦታችን የምንኮራ ጉድ ነን፡፡



በስንታየሁ (kaleb)


(ገበያ)


ፍቅር የሚሉት ብር መግዣው እንጂ ያጠረን
መገብየት ከቻልን
ሰው እኮ እቃ ነው
የገበያ ኮተት
በቅንጣት ስውር ክር
ስበው ሚሸምቱት፡፡




ቀጠሮ

እንዳትመጭ ወደኔ
ግን እርግጠኛ ነኝ እንገናኛለን፣
እዚያው በሰፈርሽ
እኔም በሰፈሬ
መንፈስ የጋራ አለን፣
ዛፉን፡ ግንቡን፡ ሀይቁን
አፈርና አየሩን
እየተመሰሉ አንችን የሚነግሩኝ
ካንች የሚያገናኙኝ
መልክተኞአሉኝ፣
እናም አንቺ መጥተ
እንዳትገናኚኝ፣
እዛው በቤትሽ ውስጥ
በሀሳብ ቅጠሪኝ፣
ስትመጭማ አልወድም
ምን ልታደርጊልኝ፣
ወትሮም ሀሳቤ እንጂ
ሀሳብሽን ያሰኘኝ፡፡
                        በ ስንታየሁ አለማየሁ




ወዳንቺ ምመጣው

አቤት፡ የሱ ስራ፡እንዲህ ነው እንዳልል፣
ታላቅ ነው፡ሚስጥር ነው፡ግዙፍ ሀያል ገድል፣
ሬቱ ሰማዩ አፈሩ ገደሉ፣
ገጽታው በሙሉ ፣
ብቻ እንደው ዝም ብሎ
አንድ ላይ ሲታዩ፡አፍዞ ያስቀራል፣
አያስቅ አያናድ
ወይ ቃል አያናግር
እንዲያው እየገፋ በምናብ ይሰዳል፣
በውስጥ ያስደምማል፡፡
በተለይ በተለይ፡ሰው መሆንን ስናይ፣
እኔ ወዳንቺ ሳይ፡አንችም እኔን ስታይ፣
ይበልጡን ይገርማል፡
ጥበብ ሁሉ አምጦ
እውቀት ሁሉ አምልጦ፡
በኛ ላይ ተወልዱል፣
የሱ መሳሪያዎች
በኔና አንች መልኮች
በኔና አንች ገጾች
ታምሩን ገልጸዋል፡፡
እናም ከሰማሽኝ፣
እናም እሺ ካልሺኝ፣
አንቺን ስመለከት ሳይሽ የምውለው፣
ገጸ በረከቱን፣
አልፋና አሜጋ
እልቆ ቢስ እውቀቱን፣
የተደረደሩ እንቁ ፊደላቱን፣
ከፊትሽ ከእጆችሽ፡ከአይኖችሽ ከእግሮችሽ፣
ከአፍንጫ ከንፈርሽ፡ከዳሌ ከጡትሽ፣
ከወገብ ከጫማሽ፡ከግንባር ከጸጉርሽ፣
ያሉትን ፊደሎች፣
ያሉትን ሆሄዎች፣
ሀሁ ለመቁጠር ነው፡፡
ቆጥሬ ቆጥሬ፡ቆጥሬም ስጨርስ፣
ከሰፊው ገበታ ፊትሽ ዕውቀት ሳስስ፣
አሁንም ከሱ ዘንድ ጥበብ ለመዝገን ነው፡፡
እናም አደራሽን
ወዳንቺ ስመጣ እንዳትሸፈኚ፣
ጨርቅ ዝባዝንኬ እንዳትከደኚ፣
ብትችይ፡ብትችይ
መላው እርቃንሽን እራቁትሽን ሁኚ፡፡
እናም እንዲያ ሳይሽ፣
ልቤ ሌላ ሽቶ ለሌላ ብፈቅድሽ፣
አንዳች እፍረት ነገር ከቶ እንዳይሰማሽ፣
አሁንም ልንገርሽ፣
ይህም የሱ ስራ ታላቅ ድንቅ ጥበብ
መሆኑን ላስረዳሽ፡፡
ብቻ ስሚኝ እቱ እውነቴን ልንገርሽ፣
ወዳንቺ ስመጣ መላ ቁመናሽን
አንችነትሽን ሳይሽ?
ልጠይቅም አይደል አግቢኝ ብየ ልልሽ፣
ልስምሽም አይደል እቀፊኝ የምልሽ፣
ግና በቃ ታምር፣
የፊደል ጋጋታ የሆሄዎች ድምር፣
ሁነሽ በማግኘቴ፣
ጥበብ ልዘግን ነው፣
እውቀት ልሰፍር ነው፣
በተራበ አንጀቴ፡፡ 
                                              በ ስንታየሁ አለማየሁ





ሀገሬ እንድልሽ




አንቺ ሁሉ እያለሽ፣
ሁሉን መሸሸጊያ መደበቂያ ሳለሽ፣
ደሀ እማይኖርብሽ፣
ላንድ ወገን ያደላሽ፣
ምን ነካሽ አገሬ፣
ምን ነካሽ አፈሬ፣
ከቶ ምን ባደርግሽ
እንዲያ እንደቀድሟችን፣
እንፋቀራለን
የማንነቴ አርማ የክብሬ መመኪያ፣
የቀለሜ አቻ የነፍሴ መለያ፣
የቋንቋዬ አንደበት፣ 
የዕውቀቴ መሰረት፣
ህይወቴ ያደገብሽ፣
ስጋዬ ያበበብሽ፣
እንገዲህ አንቺው ነሽ፣ 
አንቺ ብትተይኝ እኔ ግን ማልተውሽ፣
ቆይ ግን ምን ነክቶሽ ነው፣
እማማ እንዲሽ አርገሽ ሰው የተጠየፍሽው፣
ደሀን የረሳሽው ከእልፍኝ ያሸሸሺው፣
እሱ እኮ ነው ያኔ በየተራሮችሽ የተጋደለልሽ፣
ደምሽን ከደሙ አስበልጦ ያየሽ፣
መልክሽን ከመልኩ አመሳስሎ ያየሽ፣
በስምሽ ጊዜ ያንጎራጎረልሽ፣
ብቻ እኔ ልንገርሽ ስሚኝ እህ ብለሽ፣
ደሀው ሲጠግብብሽ ደሀው ሲያፌዝብሽ፣
ነው አንቺ ሚያምርብሽ፣
የቦርጫም ጋጋታ፣
የዘራፊ ኡኡታ፣
ሽሉ ሲያስመስል ነው ድባቅ እስኪመታ፣
እናም እባክሽን ሀገሬ እንድልሽ፣
አንቺም እንደቀድሞሽ በደንብ አቆላምጠሸ፣
ጥሪኝ ሳትፈሪ ደሀው ልጄ ብለሽ፡፡

                            በካሌብ አለማየሁ 2004




ገጣሚ እና አናፂ                                        

እኔ ቃል አልጽፍም      
                               

እሱ ቃል ይጽፋል፣
ይወትን በብእር ቀለም ይሞሽራል፣
እኔ አናፂ ነኝ፣
ህይወትን በድንጋይ ስክብ የሚያረካኝ፣
እሱ ስራው ስንኝ፣
በሀረግ ላይ ሀረግ ሰርክ እየገነባ፣
በቃሎቹ ውበት ሺ ሰው እያነባ፣
እልፍ ሰው በግጥሙ ህይወቱን ያስሳል፣
እኔ ግን ቋሚዬ፣
ማገሬ ታዛዬ፣
ሸክላ ነው ድንጋይ ነው፣
አፈር አቡክቼ ነው ውበት እምስለው፣
እናም በኔ ህንጻ በሰራሁት ግንብ ውስጥ
ሺ ሰው ተጠልሏል፣
አሸን ግፍ ከትሟል፣
እልፍ ውበት መሽጓል፣
ስለዚህ ህዝቤ ሆይ እኔና እሱ ማለት
የቅርብ እሩቆች ነን፣
የሩቅም ቅርቦች ነን፣
እኔ ቤት ስሰራ
እሱ በኔ ቤት ውስጥ የሚከራዩትን፣
ኗሪውን ይስላል፣
ህይወትን ያድላል፣
እኔ መቀበሪያ ጉድጓድ ስገነባ
እሱ ሟች ያምጣል፣
የሞተ ህይወትን አስከሬን ይነድፋል፣
እናም አናፂና ገጣሚ ሰው ማለት፣
የሚመስል አይነት እውነትና ሀሰት፣
አንዱ ስጋ ሲስል ጠፊ ከፈን ሲያበጅ፣
አንዱ ነፍስ የሚስል ህያውነት ሚያበጅ፣
እንዲያ ነው ስራቸው፣
ገጣሚና አናፂ ነገረ ግብራቸው፡፡

በካሌብ አለማየሁ

No comments:

Post a Comment